የግል ትምህርት ቤቶችን የክፍያ ጭማሪ በዘላቂነት መፍታት እንደሚገባ የትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
የተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 21ኛ መደበኛ ስብሰባ የትምህርት ሚኒስቴር የ2015 በጀት የ9 ወራት ሪፖርት ሲያደምጥ ውሏል።
የግል ትምህርት ቤቶችን የዋጋ ጭማሪ በተመለከተ በሰው ኃብት ልማት፣ ሥራ ሥምሪት እና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኩል ጥያቄዎችን ያቀረበ ሲሆን ፥ የትምህርት ሚኒስትር ብርሃኑ ነጋ(ፕ/ር) ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
በግል ትምህርት ቤቶች ለሚስተዋለው የዋጋ ጭማሪ ዘላቂ መፍትሄ መስጠት የሚቻለው የመንግስት ትምህርት ቤቶችን ማስፋፋትና ጥራታቸውን በማስጠበቅ ሲቻል እንደሆነ ነው ሚኒስትሩ የተናገሩት፡፡
ሚኒስትሩ ፥ ከግል ትምህርት ቤቶች መካከል ሚኒስቴሩ በቀጥታ የሚከታተለውና የሚቆጣጠረው በዓለም አቀፍ ደረጃ ያሉትን ትምህርት ቤቶች እንደሆነም ገልጸዋል፡፡
ከዚህ ጋር ተያይዞም በእነዚህ ትምህርት ቤቶች በዘንድሮው ዓመት ምንም ዓይነት ቅሬታ አልቀረበም ማለታቸውን ከምክር ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
ይሁንና ከእነዚህ ውጭ ያሉትን ትምህርት ቤቶች በቀጥታ የሚመለከተው ክልሎችንና የከተማ መስተዳድሮችን እንደሆነ ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡
በዚህም ችግሩን ለመቅረፍ ግን በጋራ እንሰራለን ሲሉም ነው የተናገሩት፡፡
