በምስራቃዊ ዩክሬን በምትገኘው ዲኒፕሮ ከተማ ትናንት ሌሊት [አርብ] ሩሲያ የሚሳኤል ጥቃት ፈጽማለች። በጥቃቱ የጋራ መኖሪያ ቤት እና አንድ የደኅንነት መሥሪያ ቤት ሕንጻ ኢላማ ተደርገዋል።
የከተማዋ ባለሥልጣናት እንዳስታወቁት በጥቃቱ ቢያንስ 9 ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል። ሁለቱ ሕጻናት መሆናቸው ታውቋል።
የቢቢሲ የዘገባ ቡድን በስፍራው ተገኝቶ እንዳረጋገጠው የጋራ መኖሪያ ቤት ጣሪያ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ተደርምሷል።
ንብረትነቱ የዩክሬን የደኅንነት መሥሪያ ቤት የሆነ ግዙፍ ሕንጻም የጥቃቱ ሰለባ ሆኗል
ጥቃቱን የዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዘሌንስኪ “የሩሲያ የሚሳኤል ሽብር” ብለውታል።
ዘሌንስኪ ከተደረመሰው ሕንጻ የሚወጣን ጭስ እና በጎዳና ላይ የሚንቦገቦግ የእሳት ነበልባልን በቴሌግራም ገጽ አጋርተዋል።
ክስተቱን ተከትሎ ፕሬዝዳንቱ የአካባቢው ባለስልጣናትንና የተመረጡ የካቢኔ አባላትን በመጥራት ለአስቸኳይ ስብሰባ መቀመጣቸውን ገልጸዋል።
bbc
